በባንኩና ኢቢሲ መካከል የመግባቢያ ስምምነት ተፈረመ
በኢትዮጵያ ልማት ባንክ እና በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) መካከል በሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ አብሮ ለመሥራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ታህሳስ 04 ቀን 2014 ዓ.ም በራዲሰን ብሉ ሆቴል ተፈርሟል፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት ክቡር ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) እና የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክቡር አቶ ፍስሃ ይታገሱ የመግባቢያ ስምምነቱን ፈርመዋል፡፡
በመግባቢያ ስምምነቱ መሠረት ኢቢሲ ባንኩ ለሚሰራቸው ሚዲያ ነክ ሥራዎች፣ ልዩ ልዩ መግለጫዎች እና ማስታወቂያዎች በጣቢያው /የራዲዮና የቴሌቪዥን ሚዲየሞች/ ቅድሚያ በመስጠት የዜና ሽፋን የሚሰጥ ሲሆን ባንኩም የተለያዩ ሁነቶች ሲኖሩት ለኢቢሲ ቅድሚያ በመስጠት ሽፋን እንዲያገኝ ያደርጋል፡፡
የሁለቱም ተቋማት መሪዎች ስለ ተቋሞቻቸው አጠር ያለ ጽሑፎችን አቅርበዋል፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) ባቀረቡት ጽሑፍ ልማት ባንክ የ5 ዓመት ስትራቴጂክ ነድፎ ወደ ሥራ ከገባበት በተለይም ከአንድ ዓመት ወዲህ ውጤታማ ባንክ ሆኗል፡፡ በታሪኩ ከፍተኛ የተባለ ትርፍም አስመዝግቧል፡፡ በተያዘው በጀት ዓመትም ካለፈው ዓመት የተሻለ ውጤት ለማምጣት ተግቶ እየሰራ ይገኛል፤ ምንም እንኳ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል እየተካሄደ ካለው የሠላም ማስከበር እና የህልውና ዘመቻ ጋር በተያያዘ ተግዳሮቶች ቢኖሩብንም ብለዋል፡፡
የኢቢሲ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፍስሃ ይታገሱ በበኩላቸው የሚዲያ ተቋሙ በሀገር ግንባታ፣ በሀገራዊ መግባባት እና ዴሞክራታይዜሽን ሂደት ላይ ትኩረት አድርጎ መሥራቱን ገልጸው፤ ሁለቱም አንጋፋ ተቋማት በሀገር ግንባታ ሂደት ላይ የበኩላቸውን ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ከተመሠረተ ከ113 ዓመት በላይ፣ እንዲሁ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ደግሞ ከ87 ዓመት በላይ እድሜ ያስቆጠሩ አንጋፋ ተቋማት መሆናቸው ይታወቃል፡፡
የፀረ-ሙስና ቀን ተከበረ
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ሠራተኞችና ማኔጅመንት አባላት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ18ኛ ጊዜ፣ በሀገራችን ደረጃ ደግሞ ለ17ኛ ጊዜ የተከበረውን የፀረ-ሙስና ቀን በባንኩ የመሰብሰቢያ አዳራሽ “በሥነ ምግባር የታነፀ አመራር ከሙስና ለፀዳች ኢትዮጵያ!” በሚል መሪ ቃል ህዳር 30 ቀን 2014 ዓ.ም አክብረዋል፡፡
በሥነ ሥርዓቱ ላይ የባንኩ ፕሬዝዳንት፣ ምክትል ፕሬዚዳንቶች፣ የማኔጅመንት አባላት እና ሠራተኞች የተገኙ ሲሆን ለውይይት መነሻ የሚሆኑ ጽሑፎችም ለውይይት ቀርበዋል፡፡
በሥነ ሥርዓቱ መጀመሪያ ላይ የባንኩ ፕሬዝዳንት ክቡር ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) ባደረጉት ንግግር “በሥነ ምግባር የታነፀ አመራር ከሙስና ለፀዳች ኢትዮጵያ!” በሚል መሪ ቃል በዓሉን ስናከብር እኛም በሥነ ምግባራችን የታነፅን ሆነንና ለሌሎች አርአያ በመሆን ኃላፊነታችን በአግባቡ በመወጣት የባንካችንን ሥም እና ዝና ከፍ ልናደርግ ይገባል ያሉ ሲሆን አያይዘውም በቀጣይም የባንካችን ኃላፊዎች እና ሠራተኞች በሥነምግባር የታነፁ እና ሙስናን የሚፀየፉ እና የሚታገሉ እንዲሆኑ ለማስቻል እንደ ብድር ሥራ ሁሉ የሥነ ምግባር ግንባታ ላይ በትኩረት የሚሰራ ሲሆን፣ በአጥፊዎች ላይ የሚወሰደው የእርምት እርምጃም የተጠናከረ ይሆናል ብለዋል፡፡
“የፍልስፍና ሚና በፀረ-ሙስና ጉዞ” በሚል ርዕስ በዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ እንዲሁም በባንኩ ውስጥ ሙስናና ብልሹ አሰራርን ከመከላከል አንጻር የሥነ ምግባር ክፍሉ ያከናወናቸው ተግባራት እና ሙስናና ሥነ ምግባር የወቅቱ ቁልፍ ጉዳዮች በሚል ርዕስ በአቶ ወርቁ ፈቃደ የባንኩ የሥነ ምግባርና ቅሬታ መከታተያ ቢሮ ሥራ አስኪያጅ ለውይይት መነሻ የሚሆን ጽሑፍ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎበታል፡፡
በመጨረሻም የባንኩ ፕሬዚዳንት ይህን በዓል ስናከብር ሙስናና ብልሹ አሰራር በሀገርና ተቋማት ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ በውል ተገንዝበን፣ ከመከላከል አንጻር የራሳችንን ድርሻ ወይም አስተዋጽዖ ተረድተን ኃላፊነታችንን መወጣት ይኖርብናል ያሉ ሲሆን እንደ ተቋም የኢትዮጵን ኢኮኖሚ የማሳደግ ኃላፊነት ተሰጥቶናል፡፡ ግልፅ የሆነ ራዕይና ተልዕኮም አስቀምጠናል፡፡ በዚህ ውስጥ የእኔ ድርሻ ምንድን ነው ብለን መጠየቅ ይኖርብናል፤ የባንኩ ሠራተኞችም በውሎው የተነሱ መልእክቶችን ከእለት ተእለት መደበኛ ሥራቸው ጋር በማዛመድ ተግባራዊ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡
የባንኩ ሠራተኞች ደም ለገሱ
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ሠራተኞች “ደማችንን ለጀግኖቻችን በመለገስ አጋርነታችንን እናረጋግጣለን!” በሚል መሪ ቃል የሀገር ህልውናን ለማስከበር በተለያዩ ግንባሮች እየተፋለሙ ለሚገኙ የመከላከያ ሠራዊትና በዘመቻው ላይ ለተሳተፉ ጀግኖች አለኝታነታቸውን ለማረጋገጥ ኅዳር 9 ቀን 2014 ዓ.ም በባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት ደም ለግሰዋል፡፡
የደም ልገሳ ሥነ ሥርዓቱን በንግግር ያስጀመሩት የባንኩ ፕሬዚዳንት ክቡር ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) ሲሆኑ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ሠራተኞች የሀገር ህልውናን የማስከበር ዘመቻ ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ የወር ደመወዛቸውን ከማዋጣት አንስቶ የተለያዩ ድጋፎች በማድረግ ላይ መሆናቸውን ተናግረው፤ በደም ልገሳ የቀጠለው ድጋፍ ወደፊትም ባንኩም ሆነ ሠራተኞቹ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ በማከልም ባንኩና ሠራተኞች ይህንን ሀገራዊ ጥሪ ለመመለስ ላሳዩት ተነሳሽነትና ፈቃደኝነት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በደም ልገሳ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ከ130 በላይ የባንኩ ሰራተኞች ደም ለመለገስ በፍቃደኝነት የተመዘገቡ ሲሆን ከ54 ዩኒት በላይ ደም መሰብሰቡን ለማወቅ ተችሏል፡፡
የህልውና ዘመቻው ከተጀመረ ጊዜ ጀምሮ ባንኩ ለሀገር መከላከያ ሠራዊት የብር 106 ሚሊዮን ድጋፍ ማድረጉንና 12 የባንኩ ሠራተኞች ደግሞ ግንባር ድረስ መዝመታቸው ታውቋል፡፡
የደም ልገሳ መርኃ ግብሩ ላይ በመገኘት ደም የለገሱ የባንኩ ሠራተኞች በበኩላቸው ለሀገር ህልውና በተለያዩ ግንባሮች እየተዋደቀ ለሚገኘው ጀግናው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ደም በመለገሳቸው ደስተኞች መሆናቸውን በመጠቆም ለወደፊቱም አጋርነታቸው ለማሳየት ቁርጠኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የእርሻ እና ምግብ ዓለምአቀፍ ንግድ ትርዒት በይፋ ተጀመረ
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በፕላቲኒየም ደረጃ ስፖንሰር ያደረገው 13ኛው አዲስ ቻምበር የእርሻ እና ምግብ ዓለምአቀፍ ንግድ ትርዒት፣ እንዲሁም 4ኛው አዲስ ቻምበር ዓለምአቀፍ የማኑፋክቸሪንግ እና ቴክኖሎጂ ንግድ ትርዒት ህዳር 2 ቀን 2014 ዓ.ም በአዲስ አበባ ኢግዚቢሽን ማዕከል በይፋ ተጀምሯል፡፡
በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የባንኩ የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች እንዲሁም የአዲስ አበባ ንግድ እና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የተገኙ ሲሆን ባንኩም ቦታ በመረከብ ስለሚሰጣቸው የሊዝ እና ፕሮጀክት ብድር አገልግሎቶች መረጃ ሰጥቷል፤ የህትመትና ማስተዋወቂያ ቁሳቁሶችን በማሰራጨት በሰፊው አስተዋውቋል፡፡
የንግድ ትርዒቱ ከህዳር 02-06/2014 ዓ.ም እንደሚካሄድ ታውቋል፡፡
Page 10 of 28