በባንኩ ስትራቴጂክ ሪፎርም እቅድ ዙሪያ ውይይት ተካሄደ
በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የስትራቴጂክ ሪፎርም እቅድ ዙሪያ የአንድ ቀን ወርክሾፕ በቢሾፍቱ ከተማ ኩሪፍቱ ሪዞርት ተካሂዷል፡፡
በመንግስት የልማት ድርጅቶች ይዞታና አስተዳደር ኤጀንሲ አስተባባሪነት ጥር 22 ቀን 2013 ዓ.ም በተዘጋጀው በዚህ ወርክሾፕ ላይ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገቢ፣ በጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሜቴ አባላት፣ የኤጀንሲው የስራ ኃላፊዎች፣ የባንኩ ፕሬዝዳንትና ም/ፕሬዚዳንቶች እንዲሁም ሌሎች የስራ መሪዎች ተገኝተዋል፡፡
ወርክሾፑን የኤጀንሲው የኦፕሬሽን ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ክቡር አቶ ትዕግስቱ አምሳሉ የመክፈቻ ንግግር በማድረግ አስጀምረዋል፡፡
በንግግራቸውም የወርክሾፑ ዋነኛ ዓላማ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በብድር አሰጣጥ፣ ክትትልና አመላለስ ዙሪያ ያጋጠሙትን ችግሮች በመፍታት፣ የተቋቋመበትን ተልዕኮ ለማሳካትና ኃላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት እንዲያስችለው በተቀረጸው የአምስት ዓመት የስትራቴጂክ ሪፎርም ዕቅድ ዙሪያ ለተከበረው ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ አባላት ገለጻ ማድረግ ነው፡፡
የገለጻውም አስፈላጊነት የተከበረው ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ አባላት ድጋፍና ክትትል እንዲሁም የባለድርሻ አካላት ትብብር ለተቋሙ ሪፎርም ስኬት ወሳኝ ሚና የሚጫወት በመሆኑ በሁሉም ባለድርሻ አካላት ዘንድ በባንኩ ሪፎርም ስራ ላይ ወጥ የሆነ መግባባት እንዲፈጠር ማስቻል እንደሆነ ጨምረው ተናግረዋል፡፡
በመቀጠል የባንኩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው /ፒ.ኤች.ዲ/ የተቋሙን የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ፣ ባንኩ እያከናወነ ያለውን መጠነ ሰፊ የሪፎርም ትግበራ፣ አሁን ላይ ስለሚገኝበት የለውጥ ሂደት እና ተግዳሮቶች ዙሪያ ገለጻ አድርገዋል፡፡
ገለጻውን ተከትሎ መድረኩ ለውይይት ክፍት የተደረገ ሲሆን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሜቴ አባላት ገንቢ የሆኑ ግብዓቶችንና አስተያየቶችን ሰጥተዋል፤ ላነሷቸው አንዳንድ ጥያቄዎችም ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
ከተነሱ አስተያየቶች መካከል የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በተከበረው ምክር ቤት አባላት ዘንድ የነበረው አስተሳሰብ አሉታዊ እንደነበር በዚህም የባንኩን ቀጣይነት አስመልክቶም ቀደም ሲል በምክር ቤቱ አባላት ዘንድ ጥያቄ ውስጥ የገባ እንደነበር አስታውሰው ቋሚ ኮሚቴው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ለማስረዳት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያደረገ መሆኑ ግንዛቤ ተወስዷል፡፡
በአሁኑ ጊዜ ባንኩ እያከናወነ ያለውን የሪፎርም ሥራ እንዲሁም እየሄደበት ያለው መንገድ ተቋሙን መለወጥ የሚያስችል እንደሆነ ገልጸው ሂደቱ ሊበረታታና ድጋፍ ሊሰጠው የሚገባ በመሆኑ ባንኩ እያከናወነ ያለውን የሪፎርም ሥራ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት በማሳወቅ የገጽታ ግንባታ ሥራዎችን በትኩረት ሊሰራ ይገባል ብለዋል፡፡
በተያያዘ የምክር ቤቱ የቋሚ ኮሚቴ አባላት ለባንኩ የሪፎርም ትግበራ ስኬት በየጊዜው ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እንዲሚያደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡
ክቡር አቶ ትዕግስቱ አምሳሉ በበኩላቸው የኤጀንሲው ዋነኛ ትኩረት የመንግስት የልማት ድርጅቶች ውጤታማ እንዲሆኑ ማስቻልና ማገዝ በመሆኑ ተቋማቸው የሚጠበቅበትን ክትትልና ድጋፍ ለባንኩ ያደርጋል ብለዋል፡፡
በተጨማሪም በባንኩ በኩል አሁን እየታዩ ያሉት ለውጦች የሚበረታቱ መሆናቸውን አንስተው በተከበረው ምክር ቤት አባላት የተሰጡ አስተያቶችና ግብዓቶች ተወስደው እንዲሰራባቸው አቅጣጫ ሰጥተዋል፡፡
በወርክሾፑ ማጠቃለያ ላይ የባንኩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው /ፒ.ኤች.ዲ/ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገቢ፣ በጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ አባላት ለባንኩ የሪፎርም ስራ ትኩረት በመስጠት በወርክሾፑ ላይ በመገኘታቸው ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
ባንኩ በተለያዩ ፖሊሲዎችና መመሪያዎች ዙሪያ ወርክሾፕ አካሄደ
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ከታህሳስ 09 እስከ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ቢሾፍቱ በሚገኘው የኢትዮጵያ ስራ አመራር ኢንስትቲዩት በባንኩ ፖሊሲዎችና መመሪያዎች ላይ ትኩረት ያደረገ ወርክሾፕ አካሄደ፡፡
በኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው /ፒ.ኤች.ዲ/ አወያይነት ለ6 ቀናት በተካሄደው ዎርክሾፕ ላይ የባንኩ ም/ፕሬዝዳንቶችን ጨምሮ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የስራ መሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ወርክሾፑ ላይ ውይይት ከተደረገባቸው ዋና ዋና ፖሊሲዎችና መመሪያዎች መካከል የባንኩ የብድር ፖሊሲና ፕሮሲጀር፣ የሊዝ ፋይናንሲንግ ፖሊሲና ፕሮሲጀር፣ የሰው ኃብት ፖሊሲ፣ የአይ.ሲ.ቲ ፖሊሲ፣ የግዥ ፕሮሲጀር፣ ራይት ኦፍ/ራይት ባክ /write-off/write-back/ ፖሊሲ፣ የዓለም አቀፍ የባንክ አገልግሎት ፖሊሲ፣ የትሬዠሪና ፈንድ ማኔጅመንት ፖሊሲ እንዲሁም የኢንፎርሜሽን ዲስክሎዠር ፖሊሲ ናቸው፡፡
በዚህ የቡድን ስራና ውይይት ላይ ባንኩ ለጀመረው የለውጥ እርምጃ ግብዓት መሆን የሚችሉ እና በባንኩ ውስጥ ሊሰሩ ለታቀዱ የለውጥ ስራዎች ግብዓት የሚሆኑ እንዲሁም ባንኩን የሚያዘምኑ በርካታ ሃሳቦች ተነስተው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በወርክሾፑ መዝጊያ ላይ የባንኩ ምክትል ፕሬዚዳንት ኮርፖሬት አገልግሎት አቶ ሰፊዓለም ሊበን ባደረጉት ንግግር ይህ በፖሊሲና ፕሮሲጀር ስራዎች ላይ መሰረት ያደረገው ወርክሾፕ እንዲሁም የቡድን ውይይት የባንኩን አሰራር ከማዘመን አልፎ ግልጽና አሳታፊ እንዲሆን ያስችላል ብለዋል፡፡
በውይይቱ ወቅት በየቡድኖቹ ለነበረው ትጋትና ቁርጠኝነት ምስጋናቸውን አቅርበው በዚህ የተነሳሽነት ስሜት የወርክሾፑን ግብዓቶች ወደተግባር መለወጥ ከተቻለ ባንኩን ወደተሻለ ከፍታ የማድረስ አቅም ያለው በመሆኑ ሁሉም የባንኩ አመራርና ሰራተኛ ለተጀመረው ስራ የበኩሉን አስተዋጽዖ እንዲያደርግ መልእክት አስተላፈዋል፡፡
ባንኩ በአውደ ርዕይ እና ባዛር ላይ እየተሳተፈ ነው
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ከታህሳስ 21 እስከ 27 ቀን 2013 ዓ.ም በሚቆየው ሀገር አቀፍ የአነስተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች አውደ ርዕይና ባዛር ላይ እየተሳተፈ ይገኛል፡፡
አውደ ርዕዩ “ሀገራዊ ጥሪ ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት’’ በሚል መሪ ቃል ሜክሲኮ በፌደራል አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ማስፋፊያ ባለሥልጣን ቅጥር ጊቢ ውስጥ ታህሳስ 21 ቀን 2013 ዓ.ም በይፋ ተከፍቷል፡፡
በመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ላይ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ተ/ም/ፕሬዚዳንት-አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዝ ፋይናንሲንግን አቶ ይልማ አበበን ጨምሮ የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል እና የአውደ ርዕዩ አዘጋጅ ባለስልጣን መ/ቤት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
በዚህ አውደ ርዕይና ባዛር ላይ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ምርትና አገልግሎቱን በማስተዋወቅ እና ቦንድ በመሸጥ እየተሳተፈ ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የ10 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አደረገ
በኢትዮጵያ ባንኮች ማህበር አስተባባሪነት ለሃገር መከላከያ ሰራዊት እና በጦርነቱ ለተጎዱ አካላት ድጋፍ የሚውል ገንዘብ ለማሰባሰብ የአዲስ አበባከ ተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ባደረጉት ጥሪ መሰረት ህዳር 30 ቀን 2013 ዓ.ም በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተዘጋጀው መርኃ ግብር ላይ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የ10 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አድርጓል፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) በሁነቱ ላይ በአካል ተገኝተው ድጋፉን አስረክበዋል፡፡
በመርኃ ግብሩ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ የባንኮች ማኅበር ፕሬዚዳንት እና የሃገር መከላከያ ሰራዊት ጀነራሎች የተገኙ ሲሆን ባንኮቹ ለቀረበው ጥሪ ፈጣን ምላሽ በመስጠታቸው ድጋፍ በተደረገላቸው ወገኖች ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
Page 15 of 26