ባንኩ ከዲያስፖራ ማኅበረሰብ ጋር ውይይት አካሄደ
ባንኩ የክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ጥሪን ተከትለው ወደ ሀገራቸው ከገቡ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን /ዲያስፖራ ማኅበረሰብ/ ጋር ጥር 27 ቀን 2014 ዓ.ም በባንኩ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት አካሂዷል፡፡
በውይይቱ ላይ የባንኩ ፕሬዚዳንት፣ ምክትል ፕሬዚዳንቶች፣ የዲያስፖራ ማኅበረሰብ ማህበር ተወካዮች፣ የማህበሩ አባል የሆኑ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን /የዲያስፖራ ማኅበረሰብ/ ተገኝተዋል፡፡
በውይይቱ ወቅት የባንኩ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ዮሐንስ አያሌው /ፒ.ኤች.ዲ/ ስለባንኩ የቀድሞ አሠራር፣ አሁንናዊ ሁኔታ እና ለወደፊቱ ሊሰሩ ስለታቀዱ ሥራዎች፣ እንዲሁም የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድን መሠረት በማድረግ ስለተጀመሩ የለውጥ ሂደቶች አጠር ያለ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ በጋምቤላ ክልል የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ተረክቦ ማስቀጠል ለሚችል ዳያስፖራ አስፈላጊውን ሂደት ተከትሎ መሥራት የሚችልበት ሁኔታ የተመቻቸ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በመቀጠል ለዲያስፖራው ማህበረሰብ ከባንኩ ስለሚፈልጉት እገዛ እና ተያያዥ ጉዳዮች ያሏቸውን ጥያቄዎች እንዲያነሱ መድረኩን ክፍት አድርገዋል፡፡
በውይይቱ ላይ የተገኙት ተሳታፊዎች በርካታ ጥያቄዎች እና አስተያየቶችን ያነሱ ሲሆን በዋናነትም የባንኩ የብድር አሰጣጥ ሂደትን ቀልጣፋ አለመሆን፣ የውጭ ምንዛሪ አሰጣጥ፣ የወለድ ምጣኔ እና የብድር አመላለስ፣ እንዲሁም የእፎይታ ጊዜን በተመለከተ ግልጽ የሆነ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው የጠየቁ ሲሆን ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎች ከባንኩ ፕሬዝዳንት በተሰጠው ምላሽ የባንኩ ወለድ ምጣኔ 11.5 መሆኑን ገልጸው ይህም በሃገራችን ካሉ የንግድ ባንኮች አንፃር ሲታይ አነስተኛ መሆኑ ለዳያስፖራው ጠቀሜታ እንዳለው ገልፀዋል፡፡ የእፎይታ ጊዜን በተመለከተም እንደፕሮጀክቱ ዓይነት የሚታይ ሆኖ ከ6 ወር እስከ 3 ዓመት እንደሚሆን ምላሽ ተሰጥቶበታል፡፡
ተሳታፊዎቹ ባንኩ ይህን መድረክ በማዘጋጀቱ ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን ባንኩን ባላቸው የእውቀት እና ቴክኖሎጂ ሙያ ዘርፎች የበኩላቸውን እገዛ ለማድረግ ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በጉለሌ ክ/ከ በባንኩ የገንዘብ ድጋፍ የተገነቡ የአቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች ተመረቁ
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 እና ወረዳ 8 በባንኩ የገንዘብ ድጋፍ እንደ አዲስ ፈርሰው የተገነቡ 3 የአረጋውያን እና አቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች ጥር 21 ቀን 2014 ዓ.ም ለነዋሪዎቹ ተላልፈዋል፡፡
በተዘጋጀው የቤት ምረቃ ሥነ ሥርዓት ላይ የባንኩ ፕሬዚዳትና ምክትል ፕሬዚዳንቶች እንዲሁም የጉለሌ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚን ጨምሮ ሌሎች የክፍለ ከተማውና ወረዳ አመራሮች ተገኝተዋል፡፡
Read more: በጉለሌ ክ/ከ በባንኩ የገንዘብ ድጋፍ የተገነቡ የአቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች ተመረቁ
በባንኩ የገንዘብ ድጋፍ የተገነቡ የአቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች ተመረቁ
በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የገንዘብ ድጋፍ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 5 ፈርሰው እንደ አዲስ የተገነቡ 5 የአረጋዊያንና አቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች፣ 4 መጸዳጃ ቤቶች እና 1 ምግብ ማብሰያ ቤት ጥር 14 ቀን 2014 ዓ.ም ተመርቀው የቁልፍ ርክክብ ሥነ ሥርዓት ተካሂዷል፡፡
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የባንኩ ፕሬዚዳትና ምክትል ፕሬዚዳንቶች እንዲሁም የቂርቆስ ክፍለ ከተማ እና የወረዳ 5 ከፍተኛ የሥራ አመራር አባላት ተገኝተዋል፡፡
የባንኩ ፕሬዚዳንት ዮሐንስ አያሌው (ፒ.ኤች.ዲ) በሥነ ሥርዓቱ ላይ ባስተላለፉት መልእክት ይህ ተግባር ባንኩ በማኅበራዊ ኃላፊነት ከሚያደርጋቸው መጠነ ሰፊ ድጋፎች መካከል አንዱ ሲሆን ባንኩ ከተቋቋመበት 1901 ዓ.ም ጀምሮ ማኅበራዊ ኃላፊነቱን በልዩ ልዩ መንገዶች ሲወጣ የኖረ የሀገር ሀብትና ኩራት የሆነ አንጋፋ ባንክ ነው ብለዋል፡፡
በባንኩ የገንዘብ ድጋፍ የተሰራው “ኂሩት አባቷ ማነው?” ፊልም ተመረቀ
በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የገንዘብ ድጋፍ የተሰራው በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነው ባለጥቁርና ነጭ ቀለም “ኂሩት አባቷ ማነው?” ፊልም ዲጂታላይዝ በመደረጉ ሐሙስ ጥር 5 ቀን 2014 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ሆቴል በይፋ ተመርቋል፡፡
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳር ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አበቤን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎች፣ የባንኩ ከፍተኛ አመራሮች፣ ታዋቂ አርቲስቶች እና በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ተገኝተዋል፡፡
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳር ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አበቤ ፕሮግራሙን አስመልክቶ መልእክት በማስተላለፍ ፊልሙን መርቀው የከፈቱ ሲሆን በንግግራቸውም በኢትዮጵያ የመጀመሪያው በሆነው ታሪካዊ ፊልም ላይ በመገኘታቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልፀው፣ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ለዚህ ታሪካዊ ፊልም ከመነሻው ጀምሮ እስካሁን ድረስ ላበረከተው አስተዋጽዖ አመስግነው፣ ፊልሙ በተለይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው በመጡበት ሰዓት መመረቁ ሀገራችን ከጥንት ጀምሮ በኪነጥበቡ ዘርፍ አሻራዋን ስታሳርፍ ማለፏን ከመገንዘብ ባለፈ ስለ ቀደምት የኪነ ጥበብ ስራዎች መረጃ ለማግኘትና ለቀጣይ በኪነ ጥበቡ ዘርፍ ለሚደረጉ ጥናታዊ ጽሑፎች መነሻ ግብዓትም ይሆናቸዋል ብለዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ክብርት ዶ/ር ሂሩት ካሳው በበኩላቸው በ1957 ዓ.ም በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የገንዘብ ድጋፍ የተሰራው ይህ ታሪካዊ ፊልም በወቅቱ ፊልሙ ከባንኩ በተገኘ ብድር የሰራው የሲኒማ ቤቶች አስተዳደር እዳው ተሰርዞለት ፊልሙ በስጦታ እስከተበረከተበት እለት ለ40 ዓመታት ሳይበላሽ በጥንቃቄ በማስቀመጡ ባንኩን እጅግ ያስመሰግነዋል ብለዋል፡፡
አያይዘውም በ2012 ዓ.ም ዲጂታይዝድ ተደርጎ በአሁን ሰዓት በድጋሚ ለእይታ እንዲበቃ ባንኩ ላደረገው ከፍተኛ ድጋፍ በኪነጥበብ ባለሙያዎችና በዘርፉ ሥም አመስግነው ወደፊትም ባንኩ ለዘርፉ የሚያደርገውን ድጋፍ እንደሚቀጥል ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡
ባንኩ በኢትዮጵያ የፊልም ታሪክ ግንባር ቀደም ሆኖ ፋይናንስ በማድረግ ላበረከተው አስተዋጽዖ የምሥጋና ምሥክር ወረቀት ተበርክቶለታል፡፡
Page 9 of 28